Thursday, December 24, 2015

አንዲት እህት ከሆዷ ውስጥ ጥቁር ወፍ ወጣላት

በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በደብረ ወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ እና በመካነ ጎለጎታ ቅድስት ማርያም ጠበል ሰሞኑን ከአንዲት እኅት ከሆዷ ጥቁር ወፍ ወጣላት፡፡ በክርስትና ስሟ መንበረ ማርያም ተብላ የምትጠራው እኅት ለ20 ዓመታት ያህል በሆድ ሕመማት ስትሰቃይ መቆየቷን የምትናገረው መንበረ ማርያም፤ ስቃይዋን በዘመናዊው ሕክምና ለማስታገስ ያልሔደችበት ቦታና ያልወሰደችው መድኃኒት የለም፡፡ ይሁንና የምትወስደው ሕክምና ለጊዜው ስቃይዋን ከማስታገስ በስተቀር ከሕመሟ ልትድን ባለመቻሏ ከዚህ በኋላ ይግደለኝ እንጂ ሕክም ናም ሆነ መድኃኒት መጠቀም የለብኝም፤ ብላ ጠበል ለመጠመቅ እንደ ወሰነች ትናገራለች፡፡ በውሳኔዋም መሠ ረት ወደ ወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተክርስቲያን ጠበል በመሄድ ስትጠመቅ በላይዋ ላይ የሰፈሩ 681 አጋንንት እንዳሉ በላይዋ ላይ ያደሩት የሰይጣን ሠራዊት ለፍልፎ በጥቁር ወፍ አምሳል ከሆዷ ውስጥ ሊወጣላት ችሏል፡፡ ምእመናን በዕለቱ ከሆዷ ውስጥ በትውከትነት እንደ ጥይት ተወርውሮ የወጣውን ጥቁር ወፍ ከነሕይወቱ በማየት በቪዲዮ በመቅረጽ የእግዚአብሔርን ድንቅ ተአምር እንደ መሰከሩ ተገልጿል፡፡


የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ ሰምቶ ይህንኑ ወፍ የወጣላትን መን በረ ማርያምንና ያጠመቋትን አባት ሊቀ ትጉኃን ስሙር አሐዱን በማነጋገር ድርጊቱ እንዴትና ምን ይመስል እንደነበር በሰፊው ዘግቧል፡፡

እግዚአብሔር ሥራው ድንቅ ነው፤ ተዓምሩ ዕፁብ ነው፤ ተነግሮ አያልቅም፤ ይህን ሥራውን መመስከር ደግሞ የእኛ ተግባር ነው፡፡ ለረጅም ዓመታት በሕመም ስትሰቃይ የነበረች በስመ ጥምቀቷ መንበረ ማርያም የተባለች ወጣት የእግዚአብሔርን የድንቅ ሥራው መገለጫ ሆናለች፡፡

ለዚህች እህት እግዚአብሔር ያደረገላት ገቢረ ተአምር ሲሰሙት ለጆሮ የሚከብድ፤ እንዲሁም በወቅቱ ድር ጊቱ ሲፈጸም የተመለከቱ ምእመናንን ሁሉ ያስደመመ ነበር፡፡ «ማን ያርዳ የቀበረ፤ ማን ይናገር የነበረ» ነውና ሥረ መሠረቱ ምን፣ እንዴትና መቼ ሆነ? የሚለውን ጉዳይ እሷው ባለታሪኳ እንዲህ ትተርክልናለች፡፡

«ያመኝ የነበረው ገና የአራት ዓመት ልጅ እያለሁ እሰቃይ ነበር፡፡ ለምሳሌ የራስ ምታት፣ ነስር፣ የሆድ ቁርጠት፣ የአንጀት ኢንፌክሽን ወዘተ እየተባለ በመታመም ሁልጊዜ ሐኪም ቤት እመላለስ ነበር፡፡ እናቴ እንደ ነገረችኝ የሕመሙ መነሻ ወተት ነው፡፡ «ወተት ጠጥተሽ የአንጀት ኢንፌክሽን ያዘሽ» ያለችኝ እናቴ በየክሊኒኩ እየወሰደችኝ ስታስመረምረኝ መድኃኒት እንደሚያዙልኝ አጫውታኛለች፡፡ ራሴን ማወቅ ስጀምር ትምህርት ቤት ገብቼ ስማር ሆዴን ያመኛል፡፡ በተለይ በበጋ ወራት ተምሬ ሁለት ወር ክረምት በሚሆንበት ወቅት ክፉኛ ያመኛል» ስትል ተናግራለች፡፡

መንበረ ማርያም በሕመሟ መጥናት ብዙ ጊዜ ሐኪም ቤትና ክሊኒክ ተመላልሳ እንደታከመች ገልጻል ናለች፡፡ ነገር ግን ጠበልስ አልሞከረች ይሆን? የሚለው ጥያቄ አጫረብንና ጠየቅናት፤ እርሷም ስትመልስ «በዚያን ወቅት ቤተሰቦቼ የሚያስቡት ሐኪም ቤት የሚባለውን እንጂ ጠበልን አልነበረም፡፡ እኔም ቢሆን በወ ቅቱ ጠበልን አላሰብኩትም፤ ብቻ ሐኪም ቤት ሔጄ የተለያየ መድኃኒት ይታዘዝልኛል እወስዳለሁ፡፡ ለጊዜው ያስታግሥልኛል፤ ጨርሶ ግን ሊያድነኝ አልቻለም፡፡ ይባስ ብሎ የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና ወስጄ ጥሩ ውጤት በማምጣት አራት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ ገብቼ የመጀመሪያ ዓመት መማር ስጀምር በሽታው ክፉኛ አሰቃየኝ፡፡ ያስጨንቀኛል፣ ከፍተኛ የራስ ምታት ሕመም ይሰማኛል፤ ማጥናት አልችልም ነበር፡፡ የሴሚስተር ፈተና ደርሶ ሁለት ሳምንት ሲቀረው አንደኛው ዐይኔ ውስጡ ሲቆስል ሌላኛው ዕንባ ማፍሰስ ጀመረ፡፡ ዕንባው ያለምንም ማቋረጥ ለ24 ሰዓታት ይወርዳል፡፡ ቤተሰቦቼ ሁኔታው አላምር ቢላቸው ወደ አንዲት ታዋቂ የዐይን ሐኪም ወሰዱኝ፡፡ እሷም 'በሕይወቴ እንዲህ ዐይነት ነገር ዐይቼ አላውቅም፤ ዐይኗ ውስጥ ቁስል አለና የመታት ነገር አለ ወይ?' ብላ ጠየቀች፡፡ ይሁንና ቤተሰቦቼም ሆኑ እኔ ምንም ነገር የመታኝ ነገር እንደሌለ ለዶክተሯ ነገርናት፡፡ በየሰዓቱ የሚደረግ ጠብታ አዛልኝ ለጊዜው ተሻለኝ፡፡ የከፍተኛ ትምህርቴን ግን ሳልማር ለሁለት ዓመት ያህል አቋረጥኩ» ትላለች የሕመሙን አስከፊነት የምትናገረው መንበረ ማርያም፡፡

መንበረ ማርያም እንደገለጸችልን በጤና መታወክ ሳቢያ ለጊዜው ትምህርቷን ብታቋርጥም ለትምህርቷ ያላት ቁጭት ከፍተኛ ስለነበር በሽታው መጣ ሔድ እያለ ቢያስቸግራትም ከዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በመግባት ትምህርቷን በሥራ አመራር የትምህ ርት ዘርፍ ለአራት ዓመታት ያህል ተከታትላ በ1996 ዓ.ም በዲግሪ ተመርቃለች፡፡

ይሁንና ሌላ ያላሰበችው ችግር ገጠማት፤ ይህስ ምን ይሆን? ለዚህም መንበረ ማርያም ስትናገር «የወር አበባዬ ከመጣበት ጊዜ አንሥቶ አሁን እስከዳንኩበት ጊዜ ድረስ በየወሩ በጣም እያመመኝ ክፉኛ ያሰቃየኛል፡፡ ስቃዩን ለማስታገሻ እያልኩ ፓ¬ራሲታሞል ክኒን በየአራት ሰዓት ልዩነት ሁለት ሁለት ፍሬ በመዋጥ በቀን 10 ፍሬ እወስድ ነበር፡፡ ሐኪም ቤትም ብሔድ የሚሰጡኝ መርፌ ነው፡፡ አልሻል አለኝ፡፡ የሕክምና ባለሙያዎቹ 'አግብታ ትውለድ፤ ሴቶች እንዲህ ዐይነት ሕመም ሲሰማቸው ይሻላቸዋልና መውለድ አለብሽ' ብለው አስተያየት ይሰጡኛል» ትላለች፡፡

እንደ መንበረ ማርያም አገላለጽ ብዙ ጊዜ መድኃኒትም መዋጥ ሌላ ችግር /Side-effect/ ስላለው መድኃ ኒት መውሰዱን ታቋርጣለች፤ «ከድጡ ወደ ማጡ» እንዲሉ ይባስ ብሎ በየወሩ ያማት የነበረው እንደ አዲስ የማያቋርጥ የማኅፀን ሕመም ይሰማት ጀመር፡፡ በዚህን ጊዜም በታወቁ የማኅፀን ሐኪም በመታየት በወር አበባ ሳቢያ የተነሣ በማኅፀኗ ውስጥ ትናንሽ ዕጢዎች እንዳሉ ይነገራትና የወር አበባዋ ከመምጣቱ በፊት ለአንድ ሳምንትና ከመጣም በኋላ ለአንድ ሳምንት የሚወሰድ ከባድና በጣም ውድ የሆነ መድኃኒት ይታዘዝላ ታል፡፡ ይህ የሆነው ከሁለት ዓመት በፊት ነው፡፡

«በዚህን ጊዜ የመጨረሻ ቁርጥ ውሳኔ ወሰንኩ» ትላለች መንበረ ማርያም፡፡ «መሞቴ ለማይቀር ነገር ለምን እሰቃያለሁ? በመድኃኒትስ ለምን እቃጠላለሁ?» በማለት ወደ ጠበል ቦታ ለመሔድ ወሰነች፡፡ ጠበሉን እንድትሞክር ያነሣሣትና ምክንያት የሆነቻት ደግሞ ጓደኛዋ እንደሆነች ተናግራለች፡፡ «አንድ ጓደኛዬ እንደ እኔ ዓይነት ሕመም ይሰማት ስለነበር ጻድቃኔ ማርያም ሔዳ ጠበል ጠጥታ እንደዳነች ነገረችኝ፡፡ እኔም ጠበል መጠጣትና መጠመቅ እንዳለብኝ መከረችኝ፡፡ መድኃኒቱን አቋርጬ ጠበል መጠመቅ ጀመርኩ፡፡ እየጾምኩ በተከታታይ ጠበሉን ስጠጣና ስጠመቅ በየወሩ የወር አበባዬ ሲመጣ ያመኝ የነበረውን ተወኝ፡፡ በመቀጠል ከማኅፀኔ ሥጋ ነገር ተቆርጦ ወጣ፡፡ በዚህ ጊዜ ቤተሰቦቼ «እጢው ወጣልሽ» በማለት ተአምር አሉ፡፡ ሥጋ መሰል ባዕድ አካል ከወጣልኝ በኋላ ምንም ዓይነት ስሜት ሳይሰማኝ ጤነኛ ሆንኩ፤ ጠበሉንም አቋረጥኩት» በማለት ገልጻለች፡፡

በዚህ መልኩ ለውጥ ያገኘችበትን ጠበል ስታቋርጥ ዳግም ሕመሙ ጀመራት፡፡ መንበረ ማርያም ትናገራ ለች፡፡ «ጠበሉን ለአንድ ዓመት እንዳቋረጥኩ በሽታው በባሰና በሚያስፈራ መልኩ ተመልሶ መጣ፡፡ እንደገና ጠበሉን መጠጣት ጀመርኩ፤ በዚህን ጊዜም ደጋግሞ የሆነ ነገር በሕልሜ ያሳየኛል፤ በሆነ መንገድ ላይ በጣም ጥቁርና ትልቅ ሰውዬ ዝም ብሎ ቆሞ ዐያለሁ፣ ቀጥሎ እኔ ሕፃን ልጅ ታቅፌ ሳመልጥ እሱ ትልቅ ድንጋይ ይዞ እየተከተለ በማስፈራራት ሲያሯሩጠኝ ዐያለሁ፡፡ ይህን ያየሁት በድሮው ቤታችን መገናኛ አካባቢ ነው፡፡

የመንበረ ማርያም ዋናው ታሪክ የሚጀምርው በግንቦት ወር 2001 ዓ.ም ነው፡፡ በዕለተ ሰንበት እሑድ ቀን ቅዳሴ አስቀድሳ ስትመለስ እንደተለመደው የወር አበባ ይታያትና በቃላት ሊገለጽ በማይችል ሁኔታ በጽኑ ትታመማለች፡፡ መንበረ ማርያም እንደገለጸችው «መጽሐፈ አርጋኖን ይዛ ከአንዱ ክፍል ወደ አንዱ ክፍል እየተንቆራጠጠች 'ወይኔ! እመቤቴ ኧረ አድኚኝ' እያለች መኝታ ክፍሏ ሆና ስታጣጥር በድንገት በግድግዳ ላይ የተሰቀለውን የቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ታያለች፡፡ እያጣጣርኩ በክፍሌ ውስጥ ቁጭ ብዬ ድንገት የተሰቀለውን የቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ቀና ብዬ ማየት ስጀምር የፌዝ ሳቅ መሳቅ ጀመርኩ፡፡ በዚህን ጊዜ ራሴን እየለወጠኝ ነው፤ አልፎ አልፎ እንጂ ምን እንደምሠራም አላውቅም፤ መጣሁልህ ይላል፡፡ እንደዛር ማጓራት ጀመርኩ፤ አባቴ ሲሰማ ደነገጠ፡፡ እሱ እንደነገረኝ ሁለት እጄን ይዞ የቅዱስ ገብርኤል ጠበል እየረጨ 'አንተ ማነህ?' ሲለው 'እባክህ አንተ አታውቀኝም! ዝም ብለህ ነው፤ ተቃጠልኩ ጊዜዬ ሲደርስ የምለቅበት ቀን አለ፡፡ እሷን የያዝኩት ከማኅፀን ጀምሮ ያሳደግኳት እኔ ነኝ' በማለት ለፈለፈ፡፡ በመቀጠል 'እናቷንም የገደልኩ እኔነኝ' ሲል ራሱን ገለጠ» በማለት መንበረ ማርያም አስረድታለች፡፡ እናቷ በካንሰር ሕመም ምክንያት በ1995 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውንም ገልጣልናለች፡፡

በቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ሳቢያ ማንነቱን የገለጠው ሰይጣን እንደያዛት ስታውቅ፣ የትመጠመቅ እንዳ ለባት ታስባለች፡፡ በመጨረሻም በደብረ ወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ሔዳ ጠበል መጠመቅና መጠጣት ትጀምራለች፡፡ በአምስተኛው ቀን ያደረባት ርኩስ መንፈስ መለፍለፍ ይጀምራል፡፡ በተለይ ሰኔ 10 ቀን 2001 ዓ.ም በዕለተ ረቡዕ ስትጠመቅ 681 አጋንንት እንደ ሠፈረባት ይለፈልፋል፡፡ ብዙ ሰው እንደጨረሰና አሁንም ብዙዎችን እንደያዘ ገልጾ እርሷ ላይ ሲደርስ ግን እንደተጋለጠ ተናግሯል፡፡ «ምእመናን እንደነገሩኝ ከሆነ «አንቺ ስትጮኺ እንደ አንበሳ ነው፤ የሚያስፈራና ከአንቺ የሚወጣ ድምፅ አይመስልም ብለውኛል፡፡ እኔ ግን በመሐሉ «መድኃኔዓለም መጣ» የሚል ድምፅ ሰማሁ እንጂ ራሴን አላውቅም፡፡ 

መጨረሻ ላይ ራሴን ሳውቅ ከእኔ የወጣውን ጥቁር ወፍ ይዘው አሳዩኝ፡፡ አላመንኩም፡፡ ሰው እልል እያለ 'አይዞሽ ተነሽ እመቤታችን ከነልጇ የሠራችልሽ ተአምር በጣም ድንቅ ነው፡፡ ተነሥተሽ ድንቅ ተአምሯን ትመሰክሪያለሽ' አሉ፡፡ ልብሴን ለብሼ ስወጣ ብዙ ምእመናን ቆሞ በሞባይልና በቪዲዮ የወጣውን ጥቁር ወፍ ይቀርጻል፡፡ ከሆዴ የወጣው ትልቅ አፍ ያለው ወፍ ደም ጎርሶ በሕይወት ለተወሰነ ደቂቃ ልቡ ይመታል፡፡ እኔ ራሴን አላመንኩም፤ ደስታ አይሉት ሐዘን ተደበላለቀብኝ፣ ሰውነቴ ከላይ እስከታች ይርዳል» ስትል የእግዚአብሔርን ድንቅ ተአምር መስክራለች፡፡

ሰኔ 10 ቀን ከ681 አጋንንት ውስጥ ሰማንያው ጥቁር ወፍ ሆኖ ሲወጣ ሰኔ 12 ቀን ሌሎች ቀሪዎቹ በጉንዳን መልክ ወጥተናል ብለው በመለፍለፍ ለቀቁ፡፡ በወቅቱም የጠበሉ ቦታ በጉንዳን ተወሮ እንደነበር መንበረ ማርያም ገልጻለች፡፡ ያ በሕልሟ ሲያባርራት ያየችው ጥቁር ሰው እርኩስ መንፈስ እንደሆነና ሕፃኑ ደግሞ መድኃኔዓለም ሆኖ እንዳዳናት አምና ተርጉማዋለች፡፡
መንበረ ማርያም ስለተደረገላት ድንቅ ተአምር ሰኔ 10 እና 21 ቀን 2001 ዓ.ም የእመቤታችን ክብረ በዓል ዕለት በቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቤተክርስቲያን በመድረክ ላይ ወጥታ ለሕዝበ ክርስቲያኑ መስክራለች፡፡

በመጨረሻ ያነሣንላት ጥያቄ «የተደረገልሽን ተአምር እንዴት ትገልጭዋለሽ?» ነበር፡፡ እሷም «እግዚአብሔር ያደረገልኝን ድንቅ ተአምር በቃላት ልገልጸው አልችልም፡፡ ኃያሉ እግዚአብሔር እኔን አድኖኛል ምስጋና ይድረሰው፡፡ እኔ ግን የማተኩረው ስለተደረገልኝ ተአምር መመስከር ብቻ ሳይሆን ስለማስተላለፈው ነገር ነው፡፡ ይኽም እግዚአብሔር እንዲህ ማዳን እየቻለ ሰይጣን ሊሰለጥንብን አይገባም፡፡ በሥራ፣ በትምህርት ቤትና በዕለት ተዕለት ሥራችን ላይ ውጤታማ እንዳንሆን መሰናከል እየሆነ ነው፡፡ ሕይወታችንን እያበላሸ መሆኑን አልተረዳንም፡፡ ስለዚህ ስመ ክርስትና ብቻ ይዘን መቀመጥ ሳይሆን በጾም በጸሎት እግዚአብሔርን ማገልገል ይኖርብናል፡፡ ከንስሓ አባት ጀምሮ የሃይማኖት አባቶችም ማስተማር አለባቸው፡፡ እያንዳንዱ ሰው ራሱን ይመርምር፤ ክፉ መንፈስን መዋጋት አለበት» ብላለች፡፡

«ማየት ማመን ነው» እንደተባለው በወቅቱ በደብረ ወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስና በመካነ ጎለጎታ ቅድስት ማርያም የጠበል ቦታ ሲያጠምቋት የነበሩትና ድርጊቱን የተመለከቱት ሊቀ ትጉኃን ስሙር አሐዱ ስለሁኔታው እንዲነግሩን ጠይቀናቸው እሳቸውም ታሪኩን እንዲህ አወጉን፡፡ «ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም፤ ነገሩ ተአምር ነው፡፡ ከዚህ በፊት በእርኩስ መንፈስ የታሰሩ፣ የተተበተቡ ሰዎችን በእግዚአብሔር ኃያልነትና መስቀል በመታገዝ በላያቸው ያለውን አጋንንት አስለቅቄያለሁ፡፡ ይህ ግን ልዩና በሕይወቴም ገጥሞኝ የማያውቅ ነው፡፡ በዕለቱ እኅታችን መንበረ ማርያም ወደምትጠመቅበት ክፍል ስትገባ ጀምሮ በጣም ትጮሃለች፡፡ በመስቀል እያጠመቅሁ ምንድን ነህ? ስለው አጋንንት ነን አሉ፡፡ ቀጥሎ ስንትናችሁ? አልኩት 600 አጋንንት ነን አሉና እውነቱን አውጣ ብዬ አጥብቄ ስይዘው 680 ብሎ ለፈለፈ፡፡ መጨረሻ ላይ 681ኛ ተልከስካሽ የዛር መንፈስ እንዳለ ገልጾ ከሰኔ 10 ቀን 2001 ዓ.ም ጀምሮ በተከታታይ በአራት ቀናት ውስጥ ተከፋፍሎ ወጣ» ብለዋል፡፡

እንደ እሳቸው አባባል ሰኔ 10 ቀን 2001 ዓ.ም 80ው ጥቁር ወፍ ሆኖ ሲወጣ፤ በነጋታው «593ቱ ጉን ዳን ሆኜ እወጣለሁ» ብሎ ጮኸ፤ ሲለቅ ወዲያውኑ ከየት መጣ ሳይባል አካባቢውን ጉንዳን ወረረው፡፡ በሦስተኛው ቀን ደግሞ ሰባት ሲወጣ ከሰባቱ አንዷ ብቻ ሴት ሆና ተገኘች፡፡ እሷም «ከውጭ ሀገር ነው የመጣነው፤ ሥራችን ተመሳሳይ ፆታዎችን ማጋባት ሲሆን በውጭው ዓለም አጥለቅልቀነው ወደ አፍሪካና ኢትዮጵያ በብዛት እየገባን ነው» ብላ ተናግራለች፡፡

«በመጀመሪያ ዋናውና አለቃው ' አጋንንት ጥቁር ወፍ ሆኖ ሲወጣ 600ው ሠራዊት ነኝ ብሎ ወጣ፡፡ አለ ቃውን አጋንንት» እንዴት ብለህ ነው የምትወጣው» ስለው እንደ አንበሳ አጓርቼ እወጣለሁ አለ፡፡ ልጅቷ እንደ አንበሳ እያጓራች ሳለ ጥቁር ወፍ በደም ተለውሶ ከሆዷ ውስጥ በአፏ ወጣ፤ ሲወጣም ልክ እንደ አየር ሞገድ ተወርውሮ ገንዳ ነገር ላይ አረፈ፡፡ ይህ እርኩስ መንፈስ ወፍ ሆኖ ሲወጣም ግፊት ስለነበረው እኔን ሁሉ ገፍትሮኛል፡፡ የወጣው ጥቁር ወፍ ከነሕይወቱ በመሆኑ ለተወሰነ ደቂቃ የማስካካት ድምፅ አሰምቷል፡፡ ለግማሽ ሰዓት ያህልም በሕይወት ቆይቶ ምእመናን ዐይተውታል፡፡ ድርጊቱ የሁሉንም መንገደኛ ቀልብ የሳበ ስለነበር መናፍቆች ሳይቀሩ ተመልክተው በእመቤታችን ድንቅ ተአምር ተገርመ ዋል፡፡ በተለይ አንድ ከነቀምት የመጣ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ በተአምሩ ተደንቆ ሲያለቅስ ዐይቻለሁ» በማለት ሊቀ ትጉኃን ስሙር አስረድተዋል፡፡

«አጋንንቱ መንበረ ማርያምን እንዴት እንደያዛት ስጠይቀው በተለያየ ምክንያት በይበልጥ በዛር ውላጅ ሲወርድ ሲዋረድ በዘር ሐረግ የመጣ እንደሆነ ለፍልፏል፡፡ ለ20 ዓመታት ያህል በሆዷና በማሕፀኗ ላይ ከፍተኛ ጫና በማድረስ ያሰቃያት እንደነበር ዘርዝሯል፡፡ በወር አበባዋ ጊዜ ምጥ እያበዛ ያሰቃያት እንደነበር ተናግሯል፡፡ እመቤቴ፣ እመቤቴ እያለች የእመቤታችን ማርያምን ስም እየጠራች አስቸገረችኝ እንጂ ሆዷን ኦፕራሲዮን አስደርጌ በሰበብ ልገድላት ነበር» ሲልም ተናግሯል ይላሉ፡፡

«ድርጊቱ በጣም የሚከብድ እና በእኔ ላይ የደረሰ ያህል ተሰማኝ፤ እኔም በሁኔታው በጣም ያዘንኩበትና ያለቀስኩበት ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ ድርጊት በእኔ ላይ ተከስቶ ቢሆን ኖሮ ምን ልሆን እንደምችል ትንሽ ቆም ብዬ ማሰብ ጀመርኩ፡፡ እሷ ግን እጅግ በጣም ጠንካራ፣ በእምነቷ ጽኑ ነች፡፡ በእምነቷ ጽናት እግዚአብሔር ድንቅ ሥራውን ሠራላት፡፡ አሁን ሙሉ ለሙሉ ጤነኛ ነች ብለዋል፡፡ እርኩስ መንፈሱ አባቷን ሳይቀር ሌሎች ሰዎችንም ይዣለሁ ብሎ በመለፍለፍ ልጅቷ ቤት ድረስ በመሔድ መጥተው እንዲጠመቁ ተናግሬያለሁ» በማለት ሊቀ ትጉኃን ተናግረዋል፡፡

በመጨረሻም «የማስተላልፈው መልእክት አለ፡፡ እግዚአብሔር ብዙ ሥራ ይሠራል፤ እግዚአብሔር እኛ እንድንድን የማያደርግልን ነገር የለም፡፡ ከዚች እኅት ትልቅ ትምህርት አግኝተንበታል፤ የክርስቶስ ስልጣን ይህን ዐይነት የሚሠራ ከሆነ እኛ የት ነን? ብለን ማሰብ አለብን፡፡ ትንሽም ብትሆን እምነት ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ወደ እግዚአብሔር በመቅረብ ጠበሉን፣ እምነቱን ልንጠጣ ይገባል፤ ሥጋና ደሙን ልንቀበል ያስፈልጋል፡፡ ይህ ከሆነ መዳን እንዳለ ማመን ይገባል» ሲሉ ሊቀ ትጉኃን ስሙር አሐዱ አስረድተዋል፡፡
በርግጥም መንበረ ማርያምና አጥማቂዋ ሊቀ ትጉኃን እንደገለጡት በየጠበሉ ቦታ ሲታይ በርኩስ መንፈስ በመተት፣ በዛር፣ በአጋንንትና በመሳሰሉት የተያዙ ሰዎች በእግዚአብሔር ኃይል ሲፈወሱ ማየት ጉድ ያሰኛል፡፡ ሰይጣን የምንፈራው ሳይሆን ታግለን የምናሸንፈው መሆኑን ማንም ሰው ሊያውቀውና ሊረዳው ይገባል፡፡ አውቆም በጾም በጸሎት እርምጃ ሊወሰድ ይገባል፡፡ የበለጠ ደግሞ መምህራን ሓላፊነት ወስደው ማስተማር ይኖርባቸዋል፡፡

ከእጇ ዘይት የሚፈልቅ የቅድስት ኤልሳቤጥ አስገራሚ ታሪክ

 


Tuesday, December 22, 2015

ድንቅ ተአምር - ሰሜን አሜሪካ ሚኒሶታ


ትላንት እሁድ ታህሳስ 10/2008 ዓ.ም በጾመ ነቢያትን ግዜ በደብረ ሰላም መድኃኔዓለም የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የተነገረ ተዓምር ላካፍላችሁ።

ቦታው ሰሜን አሜሪካ ሚኒያፖሊስ ሚኒሶታ ውስጥ ነው። እህታችን ዘጠኝ ወር በማሕጸኗ የተሸከመችውን ጽንስ በሰላም ተገላግላ እንደ እናት ወግ ልጇን አቅፋ ስማ ተንከባክባ ለማሳደግ ጊዜዋ ደርሶ ነበርና መያዝ የሚገባትን ነገር ሁሉ አዘጋጅታ ጨርሳ ወደ ሆስፒታል ታመራለች። በዚህ በጭንቅ ሰዓት ታድያ ካዘጋጀችው እቃዎቿ አንዱ የእናታችን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ስዕለ አድኅኖ ነበር። እህታችን ከመግባቷ በፊትም " እመቤቴ በሰላም ተገላግዬ ከቤተሰቦቼ በደስታ እንድገናኝ በሰላምም ወደቤቴ እንድገባ ከልጅሽ ከመድኅኔዓለም አማልጂኝ ጭንቁን አቅልይልኝ" ብላ ጸሎት አደረገች። ከጥቂት ጊዜም በኋላ ሴት ልጅን በሰላም ተገላገለች ሁሉም ነገር ደስታ ሆነ። ነገር ግን ይሄ ደስታ ምንም ያህል ሊቆይ አልቻለም ነበር። ባለቤቷ መታጠቢያ ክፍል ደርሶ እስኪመለስ ድረስ ነገሩ ሁሉ የተገላቢጦሽ ሆነ ያ ሁሉ ደስታ በደቂቃዎች ወደሃዘን ተለወጠ። እህታችን የወለደቻትን ልጅ እያጠባች ባለችበት ሰዓት በድንገት ራሷን ትስታለች። ወዲያው ሃኪሞች ተጠሩ ከፍተኛ እርዳታ ተደረገላት ነገር ግን መንቃት አለቻለችም። በዚህም ምክንያት በከተማዋ አሉ የተባሉ ስፔሻሊስት ዶክተሮች እና ሊሎችም ከፍተኛ የሕክምና ባለሞያዎች ቢሯሯጡም መልሱ ከነሱ አልነበረምና ምንም ሊረዷት አልቻሉም። በዚህ ጊዜ መላው ቤተሰብ በሃዘን ተዋጠ። 

በከተማው ካሉት አቢያተ ክርስቲያናት አንዱ ወደሆነው ታላቁ ደብር ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን በመምጣት ዘወትር በማሕሌት በኪዳን እንዲሁም በቅዳሴ ሰዓት በካሕናት አባቶች ጸሎት እንዲያዝላት ሽና ስሟ እየተጠራ እንዲጸለይላት
ይጠይቃሉ።ካሕናቱም በፍጹም ታዛዥነት ጽሎቱን ይጀምራሉ። እህታችን በዚሁ ሁኔታ ላይ እንዳለች ሳምንታት አለፉ። ካሕናቱም ጽሎቱን ቀጠሉ ነገር ግን አንድ ያልተጠበቀና አስደንጋጭ ነገር ተፈጠረ።የተፈጠረው ነገር ያልተጠበቀና እጅግ ተስፋ አስቆራጭ ነበር ሙሉ የሰውነት ክፍሏ ስራ አቆመ።የልብ ምቷም ቆመ። ሃኪሞቹ ተጠርተው ቢመጡም ከዚህ በላይ ምንም ማድረግ አይችሉም ነበር። ይሄን ጊዜ በሰው እጅ ያለው ተስፋ ሲሟጠጥ ሸክም ሲከብድ ቢዘገይ እንኳን የሚቀድመው የሌለው አምላክ ስራውን የጀመረው። እህታችን በእናቱ ፊት ለምልጃ ያቀረበችው ጸሎት ከዶክተሮቹ እጅ ተቀብሎ ስራውን መስራት ጀመረ። የተገጣጠሙላት መሳርያዎች ሳይነቀሉ ለስድስት ደቂቃዎች ቆሞ የነበረው የልብ ምቷ በድንግል አማላጅነት በመድኃኔዓለም ሐኪምነት ስራውን ጀመረ። ሃኪሞቹ በጣም ደነገጡ ምንም ያደረጉት ነገር ሳይኖር ለስድስት ደቂቃዎች ስራ አቁሞ የነበረው ልብ አሁን ደግሞ መስራት ጀመረ። ይሄ ከሰው ልጅ አእምሮ በላይ ነው። እስከዛሬም ሆኖ የማያውቅ ይሆናል ተብሎም የማይጠበቅ በጣም አስገራሚ ነገር ነው የተደረገው የሚል ብቻ ነበር የነሱ መልስ። ከዚህም በኋላ እህታችን ሙሉ በሙሉ ከበሽታዋ ድና እንደጓጓችለት በእመቤታችንን ምልጃ በመድኃኔዓለምን ምህረት ለዚህች ቀን ደርሳ ልጇን ታቅፋ አምጥታ ክርስትና ለማስነሳት በቃች ልጅቷም ወለተ ኪዳን ተብላ ተሰይማለች። ይህንን በሰው ሃሳብ ሲመዘን እጅግ ከባድና ከአስተሳሰባችን በላይ የሆነን ነገር ሌላ ሰው ቢናገረው እንዴት ይታመናል? በሳይንስ እይታ የልብ ምት አይደለም ለስድስት ደቂቃ ቀርቶ ለጥቂት የደቂቃዎች ሽርፍራፊ እንኳን ስራ ቢያቆም ያ ሰው ሞቷል ማለት ነበር። በሰው የተዘጋውን በር ሳይሆን በእግዚአብሔር እጅ ያለውን ቁልፍ ተመልከት እንዳሉ አቡነ ሺኖዳ ሳልሳዊ እሱ ታሪክን ቀያሪ ነውና የአራት ቀን እሬሳን ያስነሳ አምላክ ሃዘኑን በደስታ ለወጠ። የካሕናቱና የቤተሰቡ ያልተቋረጠ ጸሎት መንበረ ጸባዖት ደረሰ። አዎ በትክክልም ተደርጓል እህታችንም በአውደ ምህራት ቆማ በጸሎት ሲያስቧት የሰነበቱትን ካሕናት እና ምዕመናን አመስግና የጭንቅ ጊዜ ደራሿን ድንግልን ከምንም በላይ ደግሞ እርሱ ሐኪም እርሱ ስፔሻሊስት ሆኖ ለዚህ ያበቃትን ጌታ መድኃኔዓለምን በአንደበቷ አመሰገነች።
"ወመኑ መሐሪ ዘከማከ"
"አቤቱ እንዳንተ ያለ መሐሪ ማነው?" አይደል ያለው ሊቁ!
እህታችንን ያማለደች እመቤታችን ምልጃዋ ጸጋ ረድኤት በረከቷ አይለየን። መሐሪው አምላካችን የያንዳንዳችንን የልቡና መሻት ይፈጽምልን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!

Friday, December 11, 2015

በወረብ አብሮ የሚሳተፈው የቅዱስ መርቆርዮስ ስዕል

በጣርማበር የቅዱስ መርቆርዮስ ምስል እንዴት እንደሚንቀሳቀስ ተአምሩን ተመልከት ነጮቹ መናፍቃን ተአምሩን አይተው ደንግጠው በአድናቆት እጃቸውን በአፋቸው ይዘዋል የቅዱስ መርቆርዮስ በረከቱ ይደርብን አሜን::


 
ተአምር በ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ከርስቲያን
አባ ሳህለ ማርያም

Wednesday, December 9, 2015

የደብረ ዓሣው አባ ዮሐኒ

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
ኅዳር 5- የደብረ ዓሣው አባ ዮሐኒ የተሰወሩበት ዕለት ነው፡፡ አባታቸው አባ አሞኒም በዚህች ዕለት ነው ያረፉት፡፡ ዳግመኛም ዛሬ የቅዱስ ሌንጊኖስ ራስ የታየችበትና ተአምር ያረገችበት ዕለት ነው፡፡ 

የቅዱስ ለንጊኖስ ራስ የታየችበት ተአምር ያረገችበት ዕለት፡- ይኸውም ቅዱስ ለንጊኖስ በመጀመሪያ ጌታችንን ጎኑን በጦር የወጋው ነው፡፡ የመድኃኔዓለም የፍቅሩ መጠን ልክ የለውምና ይህንንም ጎኑን በጦር የወጋውን ሰው በወቅቱ ዕውር የነበረችውን አንድ ዐይኑን አበራለት በኋላም በስሙ አምኖ ወንጌልን ሰብኮ በሰማዕትነት እንዲያርፍ መረጠው፡፡ በሙሉ ልቡ አምኖ እስከሞት ድረስ ለመታመን ተዘጋጅቶ በክፉዎች አይሁድ ፊት ስለ ጌታችን አምላክነት መመስከር ጀመረ፡፡ አይሁድና ሮማውያንም በምስክርነቱ እጅግ ተቆጥተው ያሳድዱት ጀመር፡፡ ወደ ታናሹዋ እስያ ወደ ቀጵዶቅያ ሄዶ በዚያ ወንጌልን እንደ ሐዋርያት በመስበክ ብዙዎችን ወደ ቀናች እምነት መልሷቸዋል፡፡ አይሁድም በክፋት ተነሥተው የሐሰት ምስክር አቁመው በመኳንንት ዘንድ በሐሰት ወንጅለው በቀጵዶቅያ አገር ሐምሌ 23 ቀን አንገቱን በሰይፍ አስቆረጡት፡፡ ራሱንም ብቻዋን ወደ ኢየሩሳሌም ወሰዷት፡፡ በምስክርነቱ የቀኑና የተናደዱ በዚያ የሚኖሩ አይሁድም ራሱ ተቆርጣ ባዩአት ጊዜ እጅግ ተደስተው ከከተማ ውጭ በአንድ ኮረብታ ላይ ቀበሯት፡፡
ከብዙ ቀንም በኋላ በቅዱስ ለንጊኖስ ስብከት ያመነች አንዲት ሴት በቀጵዶቅያ አገር ራሱን ከቆረጡበት ጊዜ ጀምራ በተቆረጠበት ቦታ በመቆም ስለእርሱ ታለቅስ ነበር፡፡ ከጊዜም በኋላ ዐይኖቿ ታወሩ፡፡ የጌታችንን መቃብር ለመሳለም ተነሥታ ከነልጇ ወደ ኢየሩሳልም መጣች፡፡ ኢየሩሳልም በደረሰችም ጊዜ ልጇ ሞተ፡፡ በሀዘንም ሆና ሳለ ወደ ሀገሯ መርቶ የሚወስዳት ስላጣች መሪር ልቅሶን አልቅሳ ደክሟት ተኛች፡፡ ተኝታም ሳለ ቅዱስ ለንጊኖስን ከሞተ ልጇ ጋር በራእይ አየችው፡፡ ራሱ ተቀብራ ያለችበትንም ቦታ ነገራትና ሄዳ እንድታወጣ አዘዛት፡፡ ቅዱስ ለንጊኖስ ወዳመለከታት ወደ ቦታው ሄዳ ስታስቆፍረው መዓዛው እጅግ ጣፋጭ የሆነ የሽቱ መዓዛ ወጣ፡፡ አማኟም ሴት የቅዱስ ለንጊኖስ ራሱ ያለችበት ቦታ ስትደርስ ታላቅ ብርሃን ተገለጠላትና ዐይኖቿ በሩላት፡፡ የቅዱስ ለንጊኖስን ራስና የልጇን ሥጋ ይዛ ወደ ሀገሯ ወስዳ ባማረ ቦታ አኖረቻት፡፡ ይኸም ተአምር ኅዳር 5 ቀን የተፈጸመ ነው፡፡
/////////////////////////
አቡነ አሞኒና ልጃቸው አቡነ ዮሐኒ፡- መጽሐፍ አባታቸውን ዘስዩመ ተንቤን እሁሁ ይላቸዋል፡፡ እናታቸው ደግሞ ዓመተ መንፈስ ቅዱስ የሚባሉ ደገኛ ምግብራቸው ያማሩ ሀገር ወዳድ ናቸው፡፡ አቡነ አሞኒ የካቲት 5 ቀን አክሱም ውስጥ ሲወለዱ ሰይጣናት የወላጆቻቸውን ቤት ከበው በማየታቸው እንደተወለዱ በእጃቸው ቢያመለክቱ በአንድ ጊዜ 60 ሰይጣናት ተሸንፈው እንደጢስ በነው ጠፍተዋል፡፡ አሞኒ ማለት አሸናፊ ማለት ነው፡፡

አባ አሞኒ የራስ ፀጉራቸው ልብስ መጎናጸፊያ ሆኖላቸው የኖሩ ታላቅና ቀደምት አባት ናቸው፡፡ በደመና ተጭነው ደብረ ዘይት ድረስ በመሄድ ከአባ እብሎይ ጋር ተገናኝተው ብዙ ምሥጢርን አውርተዋል፡፡ አባ ዮሐኒን ያሳደጉት አስተምረው ያሳደጓቸው አባ አሞኒ ናቸው፡፡ የእናቱን ጡት ፈጽሞ ጠብቶ የማያውቀውን የመንፈስ ቅዱስ ልጃቸውን አባ ዮሐኒን እሳቸው እያጫወቱት የታዘዘ አሞራ በክንፎቹ እያለበሰው ቶራ (ሰሳ) እያጠባችው ነው ያደገው፡፡ መነሻ ታሪኩም እንዲህ ነው፡-

የተንቤን አውራጃ ገዥ የነበረው ሰው በዘመኑ ዐፄ ካሌብ የነበሩበት ዘመን ነበርና አብሯቸው ወደ ምድረ ኖባ ሄደው ሰባት ዓመታትን የፈጀ የጦር ዘመቻ ክርስያኖችን በሚያሠቃዩ ነገሥታት ላይ አዳሄዱ፡፡ የተንቤኑ አውራጃ ገዥም ወደ ዘመቻው ከሄደ ቆይቶ ነበርና ታናሽ ወንድሙ የገዥውን ሚስት ‹‹ወንድሜ የቀረው ሞቶ ነው እንደ ኦሪቱ ሕግ እኔው ላግበሽና ልጆቹን ላሳድግ›› አላት፡፡ እርሷም ‹‹ባሌ ቢሞት ይነገረኝ ነበረዘመቻ የሄደው ሁሉ አልተመሰም›› ብላ እምቢ ብትለው በግድ ተገናኛት፡፡ በዚህም ጊዜ አባ ዮሐኒ ተፀነሱ፡፡ በሚያዝያ 5 ቀንም ተወለዱ፡፡
ከዘጠኝ ወር በኋላ ማሏ ከዘመቻ መጣና ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡ የአካባቢውም ሰው ወጥቶ በክብር ሲቀበለው ሚስቱ ግን ምጥ ተይዛ ታማ ስለነበር ወጥታ አልተቀበለችውም፡፡ ‹‹የት ሄደች? ምንስ ሆነች?›› ብሎ ሲጠይቅ ልጅ አይደብቅምና አንድ ሕፃን ‹‹አርግዛ ልትወልድ በምጥ ላይ ትገኛለች›› አለው፡፡ የአውራጃውም ገዥ ያለችበት ድረስ ሄዶ ቢያያት ያማረ ወንድ ልጅ ታቅፋ አገኛት፡፡ ከዚህም በኋላ ከቤቱ ምሰሶ ጋር ጥፍንግ አድርግ አስሮ እየገረፋትና እያስጨነቃት ከማን እንዳረገዘች ጠየቃት፡፡ እርሷም የወንድሙን ምሥጢር ለመጠበቅና ወንድማማቾቹን ላለማጣላት ሥቃዩን ታግሳ ዝም አለች፡፡ በዚህ ቅጽበት የራማው ልዑል ቅዱስ ገብርኤል 40 ዓመት ሙሉ ዘግተው በበረሃ ለሚኖሩት ለአባ አሞኒ ተገለጠላቸው እንደ አውሎ ነፋስ አምዘግዝጎ ወስዶ አውራጃ አገረ ገዥው ቤት አደረሳቸው፡፡
እንደደረሱ ዓመተ ማርያም በጽኑ ድብደባና ግርፋት እየተሠቃየች እያለ አባ አሞኒ የጸጉራቸውን አጽፍ ለብሰው ራቁታቸውን ደጇ ላይ ቆመው አየቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ለባሏ ‹‹ያውና ከዚህ መነኩሴ ነው የወለድኩት›› አለቸው፡፡ አተንቤቱ አውራጃ አገረ ገዥውም አባ አሞኒን ይዞ ጽኑውን ግርፋት በወታደሮቹ አስገረፋቸው፡፡ በመቀጠልም ገና የእናቱን ወተት እንኳን ያልቀመሰውን ጨቅላ ሕፃን አንሥቶ ‹‹እንካ ልጅህን ይዘህ ጥፋ ከዚህ›› ብሎ ሰጣቸው፡፡ አባ አሞኒም በዚህ ጊዜ ‹‹ዮ ሀበኒ ዮ ሀበኒ›› አሉ፡፡ በትግርኛ እሽ ስጠኝ ማለት ነው፡፡ ከዚህ በመነሳት ነው ሕፃኑ በኋላ ላይ ‹‹አባ ዮሐኒ›› የተባሉት፡፡ አባ አሞኒም ሕፃኑን ተረክበው ወደ ደብረ ዓሣ ተራራ ሥር ሄደው ልጁን ከወይራ ዛፍ ሥር አስተኝተው ‹‹አምላኬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ኃጢአቴን ተመራምረህ ይህንን ሕፃን የሰጠኸኝ አላጠባው ጡት የለኝ አላበላው እህል የለኝ›› ብለው የጨቅላው ሕፃን ነገር እጅግ ቢያስጨንቃቸው ምርር ብለው አለቀሱ፡፡ ጸሎታቸውንም እንደጨረሱ ተራራውን በመስቀል ምልክት ቢባርኩት በተራራው መሐል ላይ እንደመደብ ያለ አልጋ በተአምራት ተሠርቶ አገኙት፡፡ ሕፃኑንም ከዚያ አስተኝተው ድጋሚ ጸሎት ሲጀምሩ ቶራ (ሰሳ) መጥታ እግርና እግሯን አንፈራጣ ሕፃኑን አጠባችውና ሄደች፡፡
አባ አሞኒም በዚህ ደስ ተሰኝተው ሕፃኑን ‹‹የምግብህ ነገር ከተያዘ ግዴለም›› ብለው ሌሊቱን ሙሉ ሲጸልዩ አድረው መለስ ቢሉ ዳግመኛም ሕፃኑን የታዘዘ ንስር አሞራ በክንፎቹ ጋርዶ አልብሶትና አቅፎት እንዳደረ ተመለከቱ፡፡ አባታችንም እጅግ ደስ ተኝተው እግዚአብሔርን አመሰገኑት፡፡ እንደዚሁ ሁሉ ቀን ቀን ቶራዋ እያጠባችው ሌሊት ሌሊት ንስር አሞራው አልብሶት እያደረ ሕፃኑ ሦስት ዓመት ሆነው፡፡ አባ አሞኒም ከሰባት ዓመቱ ጀምረው እስከ 12 ዓመቱ ድረስ ፊደል፣ ንባብ ከነትርጓሜው፣ ብሉይንና ሐዲስን፣ ምግባር ሃይማኖትን ሥርዓተ ቤተ ክርስያንን ሁሉ አስተማሩት፡፡
አባ አሞኒ ልጃቸው አድጎ 12 ሲሆነው ከዚህም በኋላ ዲቁና ሊያሾሙትና አክሱም ጽዮን ወስደው ሊያስባርኩት ቤተ ካህናት ከተባለው ቦታ ይዘውት ሲሄዱ ልዩ ስሙ ሲሂታ ከሚባለው ቦታ ሲደርሱ ከወገባቸው በላይ እራታቸውን የሆኑ እንስራ የተሸከሙ ዓሥር ሴቶች አገኙ፡፡ አባ ዮሐኒም አባታቸውን ‹‹አባቴ እነዚህ ደረታቸው ላይ ቀንድ ያላቸው ጽጉራቸው የረዘመ ምንድናቸው? እንደእኛ የሆኑ መስህታን የሚባሉት እነዚህ ናቸውን?›› አሏቸው፡፡ አባ አሞኒም ‹‹አይደሉም ልጄ ዝም ብለህ ሂድ›› አሏቸው፡፡ በኋላ ግን ትዝ ሲላቸው ‹‹በዱር እንስሳት ያሳደኩት ልጄ ወንድና ሴት ለይቶ ሲያውቅ በዚያው ሊሳሳት አይደልምን?›› ብለው በማሰብ ዲቁናና ክህነቱ ይቅርበት ብለው ተመልሰው ወደ በዓታቸው ይዘውት ገቡ፡፡
ከዚህም በኋላ አባ አበይዶ ወደ አባ አሞኒ መጣና እሳቸውን ከአባ ዮሐኒ ጋር እያገለገሏቸው ተቀመጡ፡፡ ዮሐኒ እየጻፈ አበይዶ የሚጻፍበትን ቆዳ እያዘጋጁ ሦስቱም በአንድነት በተጋድሎ መቀመጥ ጀመሩ፡፡
አባ ዮሐኒ 20 ዓመት አባ አሞኒ ደግሞ 40 በሆናቸው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለአባ አሞኒ ተገለጠላቸውና ‹‹አሞኒ ሆይ ከእንግዲህስ እግዚአብሔር ወደኔ ና ብሎሃል›› አላቸው፡፡ እሳቸውም ልጆቻቸውን አባ ዮሐኒንና አባ አበይዶን ጠርተው ‹‹በሉ እንግዲህ እኔ ወደ እግዚአብሔር መሄዴ ነውና ጸልዩልኝ›› አሏቸው፡፡ ከማረፋቸውም በፊት አባ ዮሐኒን ለብቻቸው ጠርተው ‹‹አንተ አባ ዮሐኒ ካሁን በፊት ሲሂታ ላይ ያየሃቸው ሴቶች ናቸው፣ አዳምንም ከገነት ያስወጡ ናቸው፡፡ ወደፊትም እንደ እነርሱ ያለ የደረሰብህ እንደሆነ ካለህበት ገደል ተወርውረህ ውደቅመ በባሕር ውስጥ ጥለቅ›› ብለው ነግረዋቸው በዛሬዋ ዕለት ኅዳር 5 ቀን በ160 ዓመታቸው በሰላም ዐረፉና ወደ ጠራቸው እግዚአብሔር ሄዱ፡፡
አባ አሞኒ ካረፉ ከ12 ዓመት በኋላ የአባ ዮሐኒ ወላጅ እናታቸው የልጇን ነገር ስታጠና ኖራ ነበርና አሁን ባሏም ስለሞተ አባ አሞኒም ስላረፉ ልጇን ልታይ ከ32 ዓመት በኋላ መጣች፡፡ ቀሚስ ለብሳ ፀጉሯን ተሠርታ በሴትነቷ ልጇ ካለበት ቦታ በመሄድ ማነጋገር እንደማትችል ስላወቀች ፀጉሯን ተላጭታ የወንድ ልብስ ቁምጣ ለብሳ በሁለመናዋ ወንድ መስላ ወደ ደብረ ዓሣ ተራራ አመራች፡፡ እዚያም እንደደረሰች በቅዱሳን ሥርዓት መሥረት ሦስት ጊዜ ‹‹አውሎ ግሶን፣ አውሎ ግሶን፣ አውሎ ግሶን›› አለች፡፡ ሰይጣን ይህን ስም ሲሰማ 40 ክንድ ይርቃል፡፡ የደብረ ዳሞ መነኮሳት እንደ ሰላምታ መለዋወጫ ይጠቀሙበታል፡፡ አባ ዮሐኒም ይህን ድምጽ ከውጭ በሰሙ ጊዜ ‹‹አንተ ማነህ?›› አሉ፡፡ እርሷም ‹‹ዓመተ መንፈስ ቅዱስ ነኝ›› አለቻቸው፡፡ አባታችንም አንድም ድምፁዋ ወትሮ ከሚያውቁት ድምፅ ስተለየባቸው ደግሞም ትዝ ሲላቸው እነዚያ እንስራ አዝለው ደረታቸው ላይ ቀንድ ያላቸው ሆነው ውኃ ቀድተው ሲሄዱ በመነገድ ያዩአቸው ሴቶች ድምፅ ሆነባቸው፡፡ ደግሞም ‹‹ወልደ እከሌ፣ ክንፈ እከሌ›› ሲባል እንጂ ‹‹ዓመተ፣ ወለተ›› ሲባል ሰምተው አያውቁም ነበርና አባታቸው አባ አሞኒ የነገሯቸው ትዝ አላቸው፡፡ በዚያውም ቅጽበት የሚጽፉባትን ብዕር ጆሮአቸው ላይ እንደሰኩ 500 ሜትር ርዝመት ካለው ትልቅ ተራራ ላይ ራሳቸውን ቁልቁል ወረወሩ፡፡ ነገር ግን መሬት ሳይደርሱ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በአየር ላይ እንዳሉ ተቀበላቸው፡፡ ብዕራቸው ግን መሬት ላይ ወድቃ ሸምበቆ ሆነች፡፡ ወዲያውም አባ ዮሐኒ ክንፍ አውጥተው ከቅዱስ ገብርኤል ጋር ጎን ለጎን ሆነው በዛሬው ዕለት ኅዳር 5 ቀን ወደ ብሔረ ሕያዋን ይዟቸው ገባ፡፡
ብሔረ ሕያዋን ያሉ እነ ሄኖክና ኤልያስም ‹‹ሰው ከሚሞትበት ሀገር ሞት ወደሌለበት አገር ማን አመጣው/›› አሉ፡፡ መልአኩም በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር ባዘዘኝ ጊዜ እኔ ገብርኤል ነኝ ያመጣሁት›› አላቸው፡፡ ቀጥሎም መልአኩ ‹‹አንተ ሄኖክ ምንም ንጹሕ ብትሆን በሥርዓተ ሥጋ ተወልደህ በሥርዓተ ሥጋ አድገህ ሚስት አግብተህ ወልደሃል፣ እግዚአብሔርም እዚህ ያደረሰህ በንፅህናህ ነው፤ አንተም ኤልያስ ምንም ድንግል ብትሆን በሥርዓተ ሥጋ ተወልደህ በሥርዓተ ሥጋ አድገህ ከዚህ ደርሰሃል፤ ይህ አባ ዮሐኒ ግን ከተወለደ ጀምሮ የእናቱን ጡት አልቀመሰም፣ ቀን ቀን ሰሳ እያጠባችው ሌሊት ሌሊት ንስር አሞራ በክንፎቹ እያለበሰው አድጓል እንጂ›› ብሎ ነገራቸው፡፡ ቀጥሎም መልአኩ የአባ ዮሐኒን ገድል ዘርዝሮ ከነገራቸው በኋላ ሊሞት ያለበትንም የአሟሟቱን ነገር ከነገራቸው በኋላ ‹‹ታዲያስ እንዲህ ያለውን አምጥቼ ከብሔር ሕያዋን ባስገባው ፍርዴ እውነት አይደለምን?›› አላቸው፡፡ ሄኖክና ኤልያስም ይህን ጊዜ ‹‹ይገባዋል›› ብለው አባ ዮሐኒን በምስጋና ተቀበሉት፡፡
ከዚህም በኋላ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ወደ ደብረ ዓሣ ተመልሶ መጥቶ ለአባ አበይዶ ተገለጠላቸውና አባ ዮሐኒን ብሔረ ሕያዋን እንዳስገባው ነገራቸው፡፡ በመጀመሪያ ሄኖክና ኤልያስ አላስገባ ብለው እንደነበርና በኋላም መልአኩ ራሱ የአባ ዮሐኒን ገድላቸውን ከነገራቸው በኋላ በምስጋና እንደተቀበሉት ለአባ አበይዶ ነገራቸው፡፡ ቀጥሎም መልአኩ የአባ ዮሐኒን ገድላቸውን እንዲጽፉትና እንዲያስተምሩበት ለአባ አበይዶ አዘዛቸውና ዐረገ፡፡ አባ አበይዶም አባ ዮሐኒ ከገደሉ ተወርውረው ሲወደቁ አንድ ደስ የሚል ወንድ ሲቀበለው አይተው ነበርና አሁን መልአኩ ሲነግራቸው እጅግ ደስ አላቸው፡፡ አባ አበይዶም በታዘዙት መሠረት የአባ ዮሐኒን ገድል ጻፉት፡፡ እርሳቸውም ትናንት ኅዳር 4 ቀን በሰላም ዐረፉ፡፡
በፎቶው ላይ እንደምታዩት ተንቤን የሚገኘው የአባ ዮሐኒ ቤተ ክርስቲያን አቀማመጡ እጅግ አስደናቂ ነው፡፡ ተራራው መሀል ላይ ወደሚገኘው ቤተ ክርስቲያኑ ለመውጣት 150 ሜትር ተራራውን መውጣት ይጠይቃል፡፡ ሽቅብ ከተወጣ በኋላ አፈ ጽዮንን ትገኛለች፡፡ ከአፈ ጽዮን በኋላ ከድንጋይ የተፈለፈለ 12 መድረክ ያለው የውስጥ ለውስጥ የጨለማ መንገድ አለ፡፡ በመጨረሻ ብርሃን ወዳለብ ስፍራ ሲወጣ በስተግራ በኩል 12 ሜትር ርቀት ላይ ቤተ መቅዱሱ ይገኛል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ 13 ጉልላቶች አሉት፡፡ ገዳሙ ጥንት 58 ዓምደ ወርቅ ነበረው፡፡ በአንድ ወቅት በመሬት መንቀጥቀጥ ምክንያት 22ቱ ሲሰባበሩ አሁን ያሉት 36ቱ ብቻ ናቸው፡፡ ገዳሙ ውስጥ ሦስት ቤተ መቅደሶች ያሉ ሲሆን አንዱን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ይቀድሱበት የነበረው ነው፡፡ ገዳሙ ደብረ ዓሣ እየተባለ ይጠራል፡፡ ምክንያቱም ቤተ ክርስቲያኑ በመሬት መንቀጥቀጥ ከመፍረሱ በፊት ጣራው የዓሣ አንበሪ ቅርጽ ነበረው፡፡ ዐፄ ገብረ መስቀልም በወቅቱ በዚህ ዓሣ ምስል ያሠሩት ቅዱስ መስቀል በገዳሙ ውስጥ ይገኛል፡፡ አንድም ደግሞ በመጀመሪያ ዐፄ ገብረ መስቀል እና ሌሎቹም ቅዱሳን አበው በገዳሙ ውስጥ ሱባኤ ገብተው ሳለ ቅዱሳን በዓሣ ተመስለው ሲወጡና ሲገቡ በማየታቸው ነው ገዳሙ ‹‹ደብረ ዓሣ አባ ዮሐኑ›› የተባለው፡፡
ሌላው በተፈጥሮአዊ አቀማመጡ እጅግ ድንቅ በሆነው በዚህ ገዳም ውስጥ አስገራሚ የመቃብር ጉድጓዶች አሉት፡፡ መቃብሮቹ የጠፈለፈሉ ዋሻዎች ናቸው፡፡ አንዱ ዋሻ በአንድ ጊዜ ከ6 ሰዎችን ጎን ለጎን አስተኝቶ መያዝ አይችልም ነገር ግን በጣም የሚገርመው የመቃብር ጉድጓዶቹ እስከዛሬም ድረስ አልሞሉም፡፡ አንድ ሰው ከተቀበረ ከዓመት በኋላ አስክሬኑ ይጠፋል፣ አጥንቱም አይገኝም፡፡ ሰሌኑ ግን እስከ ሁለት ዓመት ይቀመጣል፡፡
ለአባ ዮሐኒ ለዚህ ገደማቸው ዕጣን ጧፍ ዘቢብ የሰጠ ሰው ቢኖር ስጦታውን እንደ አቤል መሥዋዕት አድርጎ ጌታችን እንደሚቀበልለት ለጻድቁ ቃልኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡
እግዚአብሔር ቢፈቅድ በዘንድሮው በ2008ቱ ለ16 ቀን ያህል በሚደረገው የኅዳሩ የአክሱም ጽዮን ጉዞአችን ላይ ከምንሳለማቸው ከ110 በላይ ገዳማትና አድባራት ውስጥ አንዱ ይህን እጅግ ድንቅ የሆነው የአቡነ ዮሐኒ ገዳም ነው፡፡

ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ይሁን! እኛንም በአማላጅነታቸው የምንታመን የተዋሕዶ ልጆች የሆንን ሁላችንን ዛሬ ኅዳር 1 ቀን በዓመታዊ በዓላቸው አስበናቸው የምንውለውን የአባ አሞኒን፣ የአባ ዮሐኒንና የአባ አበይዶንና የቅዱስ ሌንጊኖስን ረድኤት በረከታቸውን ያሳድርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡
(ከአባ ዮሐኒ ደብረ ዓሣ ገዳም የተገኙ ጽሑፎች፣ የጥቅምትና የሐምሌ ወር ስንክሳር፣ ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ-ማኅበረ ቅዱሳን፣ ሐመር 13ኛ ዓመት ቁ.2 1997 ዓ.ም)

Tuesday, December 8, 2015

የቅዱስ ሚካኤል ተዓምር

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።
"ቅዱስ ሚካኤል በእለተ ቀኑ ያደረገው ተአምር ።"




ምስክርነቱን ስታዳምጡ የህጻናቱ እድሜ የ 6 ዓመትና የ3 ዓመት በሚለው ይስተካከል።


የቅድስት ኤልሳቤጥ አስገራሚ ታሪክ 

ባሕታዊ አባ ገብረጊዮርጊሥ በአምስተርዳም

Monday, December 7, 2015

ድንቅ ተዓምር በወይን አምባ ቅዱስ ገብርኤል - የ ተሃድሶ መንፈስ


በወይን አምባ ቅዱስ ገብርኤል በዓለ ንግስ ላይ በታቦቱ ፊት በቅዱስ ገብርኤል ከክፉ መናፍስት የተፈወሰው ወንድም:: ሰይጣን የውሸት አባት ቢሆንም "የተሃድሶ መንፈስ" ይኖር ይሆንን? በርግጥ በተለያየ ግዜ ከ መምሕር ግርማ ወንድሙ እንደተማርነው የ 666 መንፈስ እና የመናፍቅ መንፈስ የሚባል እንዳለ እርግጥ ነው:: ተሃድሶ እና የመናፍቅ መንፈስ አንድ አይነት ናቸው:: 

Testimony of a protestant pastor from east Hararge
ተአምር በ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ከርስቲያን

Memehir Girma wondimu Nequ Part 1

 

Sunday, November 22, 2015

ፀበሉ ፈዋሽ ዘብር ቅድስ ገብርኤል


በሰሜን ሸዋ ሀገር በመንዝ ላሎ ምድር (ዘብር ደብረ ምህረት ቅድስ ገብርኤል) አጭር ታሪክ ተአምረኛው ዘብር ቅድስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን የተመሰረተው በ4ተኛው መቶ ክፍለ ዘመን በውል ባይታወቅም ከቀድሞ አባቶች ሲነገር እንደቆየና እንደሚነገረው በንግስት አድሃና ዘመነ መንግስት ነው ተብሎ ይገመታል።ምክንያቱም የኦሪት ሊቀ ካህናት የእንበረም ልጅ የሕዝበ ባርክ የልጅ ልጅ አጽቀ ሌዊ በንግስት አድሐና ዘመነ መንግስት መንዝን አጥምቆ አብያተ ክርስትያናትን እንዳቀና ታሪክ ያስረዳል።

በቀደምትነት ከቀኑት፣ከተመሰረቱት እጅግ ጥቂት አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንድ ተአምረኛው ና ፀበሉ ፈዋሽ ዘብር ቅድስ ገብርኤል አንድ ነው። ደብረ ምህረት ተብሎ ስያሜ የወጣለት ይህ ቤተክርስቲያን በአሁኑ ሰአት ለ60አመት ያስተዳደሩት ሊቀ ሊቃውንት አባ አክሊሉ ከ100 አመት በላይ የሆናቸው የዕድሜ ባለፀጋ መንፈሳዊ አባት ሲሆኑ በመንዝና በሰሜን ሸዋ የአብነት ት/ቤት እንዲስፋፋ ያደረጉ ከ50,000 ሽይ በላይ የሚቆጠሩ የቤተ ክርስቲያን ጳጳሳት፣አስተዳዳሪዎች፣ካህናት፣ዲያቆናት፣መዘምራኖች ሊቃውንቶች በአቋቋም በቅኔ በድጓ ያፈሩ ለጵጵስና ተመርጠው ፣የተወለድበትን ሀገር በንጽህና በቅድስና በእውነት በማገልገል የቦታውን ቃል ኪዳን ለመጪው ትውልድ እንዲተላለፍ ያደረጉ የቤተክርስቲያን አባት በአሁኑ ወቅት አሉ። ፎቷቸው ከታች ይገኛል፣ የቦታው ቃልኪዳን የመላአኩ ቅድስ ገብርኤል ታሪኩም ሆነ ቃልኪዳኑ በድርሳኑ በተአምሩ እንዲሁም በመጽሐፍ ቅድስ ላይ ያለው እንዳለ ሆኖ ዳን•3÷24—30 ዳን•8÷15—18 ሉቃስ 1÷8—20 ለቦታው የተሰጠው ክብርና ቃልኪዳን አንድ ባህታዊ አባት መጥተው ከእየሩስሌም ብዙ ቅድሳን መላዕክትም ሳይቀሩ በቦታው ላይ በአፀዱ ላይ እንደ ንብ ስፍርውበታል ብለው ተናግረዋል፣ከዚህም በተጨማሪ በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደና የከበረ የቅድሳን አበው መናህሪያ ማረፊያ የቃልኪዳን ቦታ በመሆኑ የበዓለ ወልድና የአብነ ሃብተማርያም ገዳም ውስጥ የቅድሳን አበው አጽማቸው በመገኘቱ ነው ታሪኩ እንዲህ ነው ። አባ አክሊሉ ተማሪ ሞቶባቸው መቃብር ሲቆፍሩ አፈሩ አልቆ አንድ ወጥ ድንጋይ

 አግኘተው ሲያነሱት አንድ አባት መልካቸው የሚያምር፣ስጋቸው ያልፈረሰ ፣ፂማቸው የሚያምር መስቀላቸው ይዘው ያልቆሸሸ ንጽህ ከነመግነዛቸው ምንም አፈር ሳይነካቸው በመገኘቱ ሲሆን መቃብራቸውም ተመልሶ ተግጥሟል፣ከዚህም ሌላው የሴት መሎክሴ አጽምም ምንም ሳይሆን ተገኝቷል።12ነገ 13÷20—21 በዚህ ቦታ የሚነኘው ድህነት ይህ ተብሎ አይወሰንም በተለይ አባቶች (መስቀል፣መቋሚያ)ይዘው ፀሉት ሲያደርሱ ችግር የደረሰበት ምዕመኑ (መገበሪያ—ይዞ የተቻለውን ያህል ስንዴ፣ጧፍ፣ጣኑን፣ዘቢብን)ይዞ ቀርቦ የደብሩ ካህናት ጸሎት አድርገው ኃይል አጋንንትን ይጣልላችሁ ብለው (መስቀልና መቋሚያ ዘቅዝቀው ፀሎት ያደርጋሉ ንስሀ ገብቶ ፀሎት የተደረገለት ሁሉ ድህነት ያገኛል)። መተቱም፣አጋንቱም ይታሰራል ፣የተበደለውም ፣የተቀማውም፣የተዘረፈው፣በተለያየ አጋንት ተይዞ ሃብት ንብረቱ አእምሮው እውቀቱ የተበተነበት፣ትዳር ሰላም የሌለው፣ ከቤተሰብ ጋር የሚጋጭ፣ስራ ወይም ትዳር እንቢ ያለው የተለያየ ችግር ያለበት በቅዱስ ገብርኤል ቃልኪዳን ድህነትን ያገኛል።

የቅዱስ ገብርኤል ጽላት በአንድ አባት ራእይ ተገኘ


Tuesday, November 10, 2015

የ ኪዳነ ምሕረት ተአምር

የሚገርም የእመቤታችን ማርያም ተአምር ታሪክ ፦በራያ አልማጣ በጥሙጋ ከተማ ኪዳነ ምሕረት በተባለች ቤተክርስቲያን ለበተክርስቲያኑ ግንባታ የሚሆን ድንጋይ በመኪና ተጭኖ ከመጡት ብዙ ድንጋይ መካከል አንደኛው ድንጋይ ሲጠረብ አልጠረብም ይላል አሁንም ግንበኞቹ በተደጋጋሚ ሞከሩ ሊጠረብ አልቻለም ከዛ ሳይጠረብ ለግንባታ ሊጠቀሙበት ወደ ላይ ለመስቀል አንደኛው ግንበኛ በሁለት እጁ ተሸክሞ ወደ ላይ በሚወጣበት ጊዜ የተሸክመው ሰው እዛው ባለበት ቦታ ልክ እንደ ኤሌክትሪክ ይነዝረዋል ከዛም ከላይ ወደታች ሲወድቅበት ያ ተአምረኛ ድንጋይ ከ ሁለት ይከፈላል በጣም በሚገርም ሁኔታ ከአንደኛው ድንጋይ የምትመለከቱት የእመቤታችን ሥዕል ታየ በጣም የሚገርመው ለ 3 ዓመት መራመድ ያቃታት ሴት የድንጋዩ ፍንጣሪ እግሯን ሲመታትፈውስ አገኘች ማየት ማመን ነው ጥሙጋ እየመጣቹህ መመልከት ትችላላቹህ የእመቤታችን አማላጅነት አይለየን አሜን

Saturday, October 17, 2015

አንዳሳ ቅዱስ ጊዬርጊስ ፀበል

በደብረ መንክራት አንዳሳ ቅዱስ ጊዬርጊስ ለበርካታ አመታት ስትሰቃይ የነበረች እህታችን የቅዱስ ጊዬርጊስን ፀበል በመጠጣት እና በመጠመቅ ከሆዷ ውስጥ ሶስት መርፌ እና አንድ ምላጭ ወጦላታል። ይሂን ታምር በአይኔ በማየቴ እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ። ፀበሉ በርካታ ታምራትን እያደረገ ሲሆን በተለያዩ ደዌዎች፣በርኩሳን መናፍስት የተጠቁ ወዘተ እየተፈወሱ ይገኛሉ። ክብር ለቅዱስ
ጊዬርጊስ አምላክ ለእየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ጋር ይሁን

Thursday, October 1, 2015

ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ

ግንቦት 14- ሙሽራው ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ ከጫጉላ ቤቱ ወጥቶ የመነነበት ዕለት ስለሆነ በሀዘን የሚያስለቅሰውን ቅዱስ ገድሉን እንመለከታለን፡፡ በተጨማሪም ዛሬ የታላቁ አባት የአባ ጳኩሚስ በዓለ ዕረፍት ነው፣ ድንጋዩን እንደ ጀልባ ተጠቅመው ጣናን የተሻገሩት የአቡነ ያሳይ ዘመንደባም ዕረፍታቸው ነው፡፡
መልካም የበረከት ንባብ!!!
ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ፡- ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ ወላጅ አባቱ የቍስጥንጥንያው ንጉሥ ቴዎዶስዮስና እናቱ ንግሥት መርኬዛ በስለት ያገኙት ብቸኛ ልጃቸው ስለሆነ ሃይማኖትን እያስተማሩት በምግባር በእጅጉ ተንከባክበው አሳድገውታል፡፡
የአባቱን ንግሥና በመውረስ ቍስጥንጥንያን እንዲገዛላቸው በመፈለግ ወላጆቹ ለአካለ መጠን ሲደርስ የሮሙን ንጉሥ ሴት ልጅ አጋቡት፡፡ እርሱ ግን ዓለምን ፍጹም በመናቅ የክርስቶስን መስቀል ለመሸከም የተዘጋጀ ነበርና የሠርጉ ዕለት ሌሊት የእርሱንም ሆነ የሙሽይቱን ድንግልና እንደጠበቀ ከጫጉላ ቤት ወጥቶ በመርከብ ተሳፍሮ ሩቅ ሀገር በመሄድ በቤተክርስቲያን ተቀምጦ ከነዳያን ጋር ተደባልቆ በመለመን ለምኖ ያገኘውንም ለሌሎች እየመጸወተ በጾም በጸሎት ተጠምዶ 15 ዓመት ኖረ፡፡
እመቤታችን ተገልጻ ለአንድ የቤተክርስቲያኑ አገልጋይ የገብረ ክርስቶስን ጽድቅ ብትነግረው ምሥጢሩን ለሀገሩ ሁሉ አዳረሰበት፡፡ ሙሽራው ገብረ ክርስቶስም ‹‹ግብሬ ታወቀ፣ ከዚህ ውዳሴ ከንቱ ልሽሽ›› በማለት ወደሌላ ሀገር በመርከብ ሲጓዝ ፈቃደ እግዚአብሔር መርከቢቱን ያለ አቅጣጫዋ ወስዶ አባቱ ደጅ አደረሰው፡፡ ማንነቱን እንደደበቀና ዓለምን ምን ያህል እንደናቃት ይረዳ ዘንድ በአባቱና በንጉሡ ደጅ የኔ ቢጤ ለማኝ ሆኖ ለአባቱ ውሾች የሚሰጠውን ፍርፋሪ እየተመገበ አሁንም 15 ዓመት ሙሉ በትዕግስት ተቀመጠ፡፡
የአባቱ አሽከሮች እንኳን እጣቢና ቆሻሻውን ሁሉ እየደፉበት ሲያሠቃዩት የአባቱ ውሾች ግን የእግሩን ቁስል ይልሱለት ነበር፡፡ በአጠቃላይ ገብረ ክርስቶስ እጅግ የተከበረ የታላቅ ንጉሥ ልጅ ሲሆን ነገር ግን ዓለምን ፍጹም በመናቅ ስለ ጽድቅ ተሰዶ እየለመነ ያገኘውን እየመጸወተ በጾም በጸሎት እየተጋደለ 30 ዓመት ሙሉ ተቀመጠ፡፡ በመጨረሻም ጌታችን እመቤታችንን፣ ቅዱሳን መላእክትን ሁሉ፣ ከገብረ ክርስቶስ በፊት የነበሩ ነቢያትን ሁሉ፣ ሐዋርያትን፣ ጻድቃንን፣ ሰማዕታትን ሁሉ አስከትሎ መጥቶ ቃልኪዳን ከገባለት በኋላ ከጌታችን ጋር አብረውት የመጡት ሁሉ በታላቅ ክብርና ምስጋና እያመሰገኑት ጌታችን ክብርት ነፍሱን በእቅፉ ተቀብሎ አሳርጓታል፡፡
የቁስጥንጥንያው ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ በቅዳሴ ላይ ሳሉ ከንጉሡ ቤት ሄደው የገብረ ክርስቶስን ሥጋ እንዲያመጡ የእግዚአብሔር ድምፅ ከሰማይ በትእዛዝ መጣላቸውና ሄደው ቢያዩ የገብረ ክርስቶስን ሥጋ በንጉሥ አባቱ ደጅ ወድቆ አገኙት፡፡ በገብረ ክርስቶስም እጅ ላይ በጥቅል ወረቀት የተጻፈ ደብዳቤ ነበርና ወስደው ሊያነቡት ሲሞክሩ ወረቀቱ አልላቀቅ ብሎ ፈጽሞ እምቢ አላቸው፡፡ ብዙ ምሕላና ጸሎት ከተደረገ በኋላ ወረቀቱ ከእጁ ላይ ተላቀቀና ሲነበብ ገብረ ክርስቶስ ስለ አምላኩ ፍቅር ብሎ ለ30 ዓመታት ያሳለፈውን እጅግ አሠቃቂ መከራ በተለይም በአባቱ ደጅ ማንም ሳያውቀው ያሳለፈውን እጅግ አሳዛኝ መከራና በኀዘን የሚያስለቅሰውን ታሪኩን በራሱ እጅ በዝርዝር ጽፎት ተገኝቷል፡፡ ንጉሡ አባቱና ንግሥት እናቱም ይህንን ልጃቸው የጻፈውን መልእክት ባነበቡ ጊዜ የሚሆኑት ጠፋቸው፡፡
በጣም የሚገርመው ደግሞ ወላጆቹ ሚስት አድርገው ያመጡለት የሮሙ ንጉሥ ሴት ልጅ ለባሏ ታማኝ ሆና 30 ዓመት ሙሉ በእናት አባቱ ቤት በትዕግስት ስትጠብቀው መኖሯ ነው፡፡ እርሷም ታሪኩ ሲነበብ ብትሰማ እንደ ዕብድ ሆነች፡፡ የቅዱስ ገብረ ክርስቶስን ሥጋውን ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዱ እጅግ አስገራሚ ተአምራት በድውያን ሕመምተኞች ላይ ተፈጽሟል፡፡ ከተአምራቱ የተነሣ መንገዱ በሕዝብ ተጨናንቆ አላሳልፍ ቢላቸው ንጉሡ በመንገድ ዳር ወርቅ እየበተነ ሰው ወርቁን ለማንሳት ሲሄድ በፍጥነት ወደ ቤተ ክርስቲያን አድርሰውታል፡፡ ዕረፍቱም ጥቅምት 14 ቀን ሲሆን ዛሬ ከጫጉላ ቤቱ መንኖ የወጣበት ዕለት ነው፡፡
አቡነ ያሳይ ዘማንዳባ፡- የደብረ በንኰል ገዳም አበምኔት አቡነ መድኃኒነ እግዚእም በአንድ ቀን ለሰባት አባቶች የምንኵስናን ልብስ አልብሰዋቸል፤ አስኬማ ዘመላእክትን አስታጥቀዋል፡፡ እነዚህም ሰባት ታላላቅ አባቶች "ሰባቱ ከዋክብት" በመባል የሚታወቁት ናቸው፡፡ እነዚህም አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ፣ አቡነ ሳሙኤል ዘቆየፃ፣ አቡነ ሳሙኤል ዘጣሬጣ፣ አቡነ ያሳይ ዘማንዳባ፣ አቡነ ዮሐንስ ዘጉራንቋ፣ አቡነ ታዴዎስ ዘባልተዋር እና አቡነ ያፍቅረነ እግዚእ ዘጉጉቤን ናቸው፡፡ እነዚህም 7ቱ ከዋክብት ከተሰዓቱ (ከዘጠኙ) ቅዱሳን በኀላ መላዋን ኢትዮጵያ በወንጌል ያዳረሱ ታላላቅ ቅዱሳን ናቸው፡፡ አቡነ ያሳይ ዘማንዳባም አንዱ ናቸው፡፡
ጻድቁ ድንጋዩን እንደ ጀልባ ይጠቀሙበት ነበር፡፡ የማንዳባው አቡነ ያሳይ የመድኃኔዓለምን ታቦት ይዘው ወደ ደሴቲቱ የገቡት ትልቁን ድንጋይ እንደ ጀልባ ተጠቅመው በድንጋዩ ላይ ተቀምጠው የጣናን ሐይቅ እየቀዘፉ ነበር፡፡ ትልቁ ጠፍጣፋ ድንገይ ዛሬም ድረስ በገዳማቸው ውስጥ በክብር ተቀምጦ ይገኛል፡፡
ጻድቁ በይበልጥ የሚታወቁት በ"አትማረኝ ዋሻ" ታሪክ ነው፡፡ በገድላቸው ተጽፎ እንደሚገኘው ዋሻው በጣና ሐይቅ ደሴቶች መካከል ከሚገኙ ገዳማት መካከል ከማን እንደ አቡነ ያሳይ መድኀኔዓለም አንድነት ገዳም በስተ ምእራብ አቅጣጫ የጣና ሐይቅን ጉዞ ከገታው አንድ ተራራ ሥር የሚገኝ ነው፡፡
ጻድቁ ከእግዚአብሔር በተሰጣቸውም ጸጋ በጣና ሐይቅ ላይ እንደ ጀልባ በሚጓዙበት አንድ ጠፍጣፋ ድንጋይ ተቀምጠው በጣና ደሴት ላይ ለአገልግሎት በመፋጠን ላይ እያሉ ዛሬ አትማረኝ ዋሻ ተብሎ ወደሚጠራው አካባቢ ሲደርሱ አንድ አባት ዋሻው ውስጥ “አትማረኝ፣ አትማረኝ፣ አትማረኝ” እያሉ ሲጸልዩ ያገኟቸዋል፡፡ አቡነ ያሳይ በሰውዬው ጸሎት በመገረም ቀርበዋቸው “አባቴ ምን ዓይነት ጸሎት ነው የሚጸልዩት? ይበሉ ከዛሬ ጀምረው “ማረኝ” እያሉ ይጸልዩ" በማለት አቡነ ዘበሰማያትን አሰተምረዋቸው ይሄዳሉ፡፡ አትማረኝ እያሉ ይጸልዩ የነበሩት አባትም “ማረኝ” እያሉ መጸለያቸውን ቢቀጥሉም ብዙ መግፋት ሳይችሉ ጸሎቱ ይጠፋባቸዋል፡፡ ጸሎቱን ያስጠኗቸው አባት አቡነ ያሳይ በድንጋዩ ላይ ተቀምጠው ጣናን አቋርጠው ርቀው ሳይሄዱባቸው ከኀላ በውኃ ላይ በባዶ እግራቸው እየተራመዱ በመከተል ይደርሱባቸዋል፡፡ “አባታችን ያስጠኑኝ ጸሎት ጠፋብኝ፡፡ እባክዎ እንደገና ያስተምሩኝ” ይሏቸዋል፡፡ አቡነ ያሳይ የእኚህ አባት መብቃት (በባሕር ላይ በባዶ እግራቸው መራመዳቸውን) ተመልከተው “አባቴ እግዚአብሔር የልብ ነውና የሚመለከተው እንዳስለመዱት ይጸልዩ የእርስዎ ይበልጣል” ብለዋቸው ይሔዳሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ቦታው አትማረኝ ዋሻ ተብሎ ተጠርቷል፡፡
አቡነ ያሳይ እጅግ አስገራሚ ተአምራትን በማድረግ ወንጌልን በሀገራችን ያስፋፉ ሲሆን ተጋድሎአቸውን ፈጽመው ከጌታችን ታላቅ ቃልኪዳን ተቀብለው በዛሬዋ ዕለት ዐርፈዋል፡፡ በረከታቸው ይደርብን!
ኃያል መነኮስ አባ ጳኩሚስ፡- በሥርዓተ ምንኵስና ታሪክ ሌላውን ታላቅ ሥፍራ የያዘው ደግሞ የአባ እንጦንስ ደቀ መዝሙር የነበረው አባ ጳኩሚስ ነው (23ዐ-346 ዓ.ም)፡፡ አባ ጳኩሚስ ግብፅ ውስጥ ኤስና በምትባል መንደር ከአረማውያን ቤተሰቦች በ29ዐ ዓ.ም ተወለደ፡፡
በቆስጠንጢኖስ ዘመነ መንግሥት ለውትድርናም ተመልምሎ አገልግሎት ሰጥቷል፡፡ በውትድርናው ዘመን የክርስቲያኖችን ቆራጥነት፣ ደግነትና ርኀራኄ በማየቱ ልቡ ስለተነካ ግዳጁን ፈጽሞ ሲመለስ በ313 ዓ.ም የክርስትናን እምነት ጠንቅቆ በመማር አምኖ ተጠመቀ፡፡ የአባ ጳኩሚስ ልቡና የቅዱስ እንጦንስ ደቀ መዝሙር በነበረው በአባ ጴላጦንስ ኑሮ ስለተማረከ ወደ በረሃ ወርዶ የብሕትውናን ኑሮና ሥርዓት ሲማር ከቆየ በኋላ በ32ዐ ዓ.ም በዓባይ ወንዝ አጠገብ ታቤኒስ ከተባለው ቦታ የራሱን ገዳም መሠረተ፡፡
እዚህ ጋር የመነኮሳትን ትውልድ መመልከቱ ተገቢ ይሆናል፡፡ ርዕሰ መነኮሳት የሆኑት አቡነ እንጦንስ በእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ ምንኩስናን ከሊቀ መልአኩ ከቅዱስ ሚካኤል እጅ ተቀበሉ፡፡ እንጦንስም ታላቁ መቃርስን አመነኮሷቸው፤ ታላቁ መቃርስም ጳኩሚስን አመነኮሷቸው፤ እንዲህ እንዲህ እያለ የአባቶቻችን የምንኩስና ትውልድ እስከ ጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት የደረሰ ሲሆን እሳቸውም ያመነኮሷቸው እጅግ ብዙዎች ናቸው፡፡



ጳኩሚስም ቴዎድሮስን፣ ቴዎድሮስ ደግሞ አቡነ አረጋዊን(ዘሚካኤልን)፣ አረጋዊ ክርስቶስ ቤዛነን፣ ክርስቶስ ቤዛነ መስቀል ሞዐን፣ መስቀል ሞዐ ዮሐኒን፣ ዮሐኒ ኢየሱስ ሞዐንና ተክለ ሃይማኖትን(በቆብና በአስኬማ)፣ ኢየሱስ ሞዐ
ተክለ ሃይማኖትን(በቅናትና በቀሚስ)፣ ተክለ ሃይማኖት ኢየሱስ ሞዐን (በቆብና በአስኬማ) ወልደዋል፡፡
ዻኩሚስ መጀመሪያ ወደ ምንኩስናው ዓለም የመጣው በታላቁ አባ ዸላሞን አማካኝነት ነው፡፡ ለተወሰነ ጊዜም መንፈሳዊ አባቱን እየረዳ ሕይወተ መነኮሳትን አጥንቷል፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወቱና በተጋድሎ እየበረታና እየደረጀ ሲሔድ ከአባ ዸላሞን ተለይቶ ማሕበር መስርቶ ለመኖር አምላኩን ጠይቆ ፈቃድ በማግኘቱ በሕግ የሚመራ የመጀመሪያውን ገዳም መሥርቷል፡፡
ቅዱስ ዻኩሚስ ጸሎቱ አጋንንትን ከአካባቢው አያስቀርባቸውም ነበር፡፡ አካሉ አልቆ በአጥንቶቹ እስኪቆም ድረስ ጾሟል፡፡ ዓርብ ዓርብ የጌታችንን ሕማማት እያሰበ ከእንባ ጋር ይሰግዳል፡፡ እንባውና ላበቱ ከፊቱ እየወረደ አካባቢው ጭቃ ይሆን ነበር፡፡ ጌታችንም መስቀል ተሸክሞ ይታየው ነበር፡፡ አባ ጳኩሚስ ሲሰግድ ወዙ ወርዶ መሬቱን ጭቃ አደረገው፣ ወዲያው ጌታችን ተገለጸለትና ጳኩሚስ "አንተን አገኝ ብዬ እንዲህ እደክማለሁ" አለው ጌታችንም "እኔም እንጂ ላንተ ብዬ እንዲህ ሆኜ ተሰቅያለሁ" ብሎ በዕለተ ዓርብ እንደተሰቀለ ሆኖ ጐኑን እንደተወጋ ደሙ እንደፈሰሰ ሆኖ ታይቶታል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን በበረሃ ሳለ መልአክ መጥቶ በነሐስ የተጻፈ ሕግ ሰጠው እርሱም በዚሀ የመጀመሪያውን ሥርአተ መነኮሳትን አዘጋጅቷዋል። ከዚህም ባለፈ በርካታ ሥራዎችን ሠርቷል፡፡ ቅዱስ ዻኩሚስ ጫማ ሳይጫማ እሾህን ሳይሰቀቅ ይረግጥም ነበር፡፡
አባታችን ቅዱስ ዻኩሚስ ከርሕራሔው የተነሣ አጋንንት ያደሩባቸውን ሰዎች ሲያገኝ በቀጥታ ከመፈወስ ይልቅ ደዌውን ርኩሳን መናፍስቱንም ወደ እርሱ እንዲገለበጡ ያደርግ ነበር:: ከዚያም በጾም በጸሎትና በስግደት መድረሻ ያሳጣቸዋል፡፡ ያንጊዜ በግዳቸው እየጮሁ ሲወጡ ደጉ አባት "ምነው ትንሽ ቆዩ እንጂ" እያለ ይቀጣጠብባቸዋል፡፡ አንድ ዕለት ቅዱስ ጳኩሚስ አንዲት ሴት ብዙ አጋንንት ሰፍረውባት ስትሰቃይ አየና "አቤቱ ጌታዬ ሆይ ይህን ሁሉ እንዴት ትችለዋለች?" ብሎ በእርሷ ላይ ያለውን የአጋንንት መንጋ ወደ እርሱ እንዲገለበጥ ፈጣሪውን ለመነ፡፡ በዚህ ጊዜ በአንድ ቀፎ ውስጥ ያሉ ንቦች ወደ ሌላ ቀፎ እንደሚገለበጡ እነዚያ አጋንንት በሙሉ ከዚያች ሴትዮ ወጥተው በአባ ጳጉሚስ ላይ ሰፈሩ፡፡ እርሱም ማቅ ለብሶ አመድ ነስንሶ በሥግደት በጾምና በጸሎት አሰቃያቸው፡፡ የዚህን ቅዱስ አባት ትሩፋትና ተጋድሎ ስላልቻሉ አጋንንቱ "እንሂድ እንጂ እንግዲህማ ምን እናደርጋለን" ሲሉ ሰማቸው፡፡ ቅዱስ ጳኩሚስም "ለምን አትቆዩም ሰው እንዲህ ካለ ኃጥእ ወዳጁ ቤት እኮ ጥቂት ጊዜ ያርፋል" ቢላቸው "እኛስ ከገነት ካስወጣነው ከአዳም በቀር እንዲህ ያለ ሰው አላየንም ትሩፋቱ አቃጠለን ሊያስቀምጠን አልቻለም" ብለው መስክረውለት ሄዱ። (ኤፌ.6፥11 "የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ።")
አባ ዻኩሚስ ስለ ክብራቸው መልአክ ነጥቆ ወስዷቸው ገነትንና ሲኦልን አሳይቷቸው መልሷቸዋል።
በዙሪያው ለተሰበሰቡት መነኰሳትም የአንድነት ኑሮ ሕግ አወጣላቸው፡፡ ምንኩስና በእግዚአብሔር ፈቃድ በአባ እንጦንስ ቢመሠረትም ሕይወቱን በማስፋፋት ደረጃ የቅዱስ ዻኩሚስን ያህል የደከመና የተሳካለት ግን የለም፡፡ በአባ እንጦንስ ለተጀመረው የማኀበረ መነኰሳት ኑሮ የተጠናከረ ሥርዓት አውጥቶ የበለጠ ከማስፋፋቱም በተጨማሪ ዘጠኝ የወንድና ሁለት የሴቶች ገዳማት መሥርቷል፡፡ አባ ጳኩሚስ ያወጣው የመነኰሳት የአኗኗር ሕግ ዋናው ቅጂ ሲጠፋ ወደ ላቲን የተተረጐመው ግን እስከዛሬ ድረስ ይገኛል፡፡ ከሕግጋቱ መካከል፡-
፩. መነኮሳት ጠዋትና ማታ በማኀበር እንዲጸልዩ
፪. በኀብረት በአንድነት እንዲሠሩ
፫. ቅዱሳት መጻሕፍትን አዘውትረው እንዲመለከቱ
፬. መነኮሳት ሹመት እንዳይሾሙ ከልክሏል
፭. መነኮሳት የቁም ጽሕፈት እንዲማሩ
፮. ገቢና ወጪአቸው አንድ ላይ እንዲሆን
፯. መነኮሳት በአንድነት እንዲመገቡ
፰. አንድ ዓይነት ልብስ እንዲኖራቸው
፱. መነኮሳት ንጽሕናቸውን ጠብቀው እንዲኖሩ
፲. ከግብፅ ውጪ ምንኩስናን ያስፋፉ አባቶችን አስተምሮ አመንኩሷል፡፡ (ለምሳሌ በኢትዮዽያ ምንኩስናን ያስፋፉት አቡነ አረጋዊ የዚህ አባት ደቀ መዝሙር ናቸው)
፲፩. መነኮሳት ከገዳማቸው በፍጹም እንዳይወጡ ከልክሏል
፲፪የመጀመሪያውን ሥርዓተ መነኮሳት አዘጋጅቷል
፲፫. መነኮሳት ደግነት፣ ፍቅርና ታዛዥነት እንዲኖራቸው...የሚሉት ይገኙበታል፡፡
አንድ ሰው ወደ ገዳማቱ ሲመጣ የሦስት ዓመት አመክሮ ይሰጠውና ጠባዩና ፍላጐቱ ይገመገማል፡፡ ከዚያ በኋላም ብርታቱና ጽናቱ ታይቶ ወደ ማኀበረ መነኰሳቱ ይቀላቀላል፡፡ አባ ጳኩሚስ በዚሁ ዓይነት መንገድ ሥርዓት ሠርተው ሕግ አጽንተው ገዳማትን ካስፋፉና አበምኔት ሁነው 40 ዓመት ካገለገሉ በኋላ ከጌታችን ቃልኪዳን ተቀብለው ለደቀመዛሙርቶቻቸው ቴዎድሮስ ሹመውላቸው በተወለዱ በ56 ዓመታቸው በ346 ዓ.ም በሰላም ዐርፈው ቅድስት ነፍሳቸውን ጌታችን በክብር ተቀብሏታል፡፡
የቅዱሳኑ በረከት በአማላጅነታቸው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን አሜን! ይልቁንም እኔን ኀጥኡን ምልጃቸው ሥርየተ ኃጢአትን ያሰጠኝ!!
(ምንጭ፡- ገድለ ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ፣ ገድለ አቡነ ያሳይ-ያለታተመና በገዳሙ የሚገኝ፣ ስንክሳር ዘወርሃ ግንቦት፣ የቅዱሳን ታሪክ፣ መዝገበ ታሪክ)